አላህንﷻ ለሰው ልጆች በሚያስተዋውቁ መልክተኞች (ሩሱል) ማመን፦

አላህንﷻ  ለሰው ልጆች በሚያስተዋውቁ መልክተኞች (ሩሱል) ማመን፦
አላህﷻ ባሮቹን እንዲሁ ለከንቱ አልፈጠራቸውም። ለዚህም ነው እርሱነቱን፣ኃያልነቱን፣ምሉእነቱንና ሕግጋቱን የሚያስተዋውቁ መልክተኞችን ወደ ሰው ልጆች የላካቸው። ከሰው ልጆች መካከል ብልጫና ትሩፋት ያላቸውን መርጦ መልክቱን እንዲያደርሱ መልክተኞቹ አድርጎ ልኳቸዋል። ከመልክተኞቹ መካከል ኑሕ፣ኢብራሂም፣ሙሳና ዒሳ ሲገኙ አለህ መልእክቱን ያጠቃለለው በመልክተኞቹ ቁንጮና በላጫቸው በሆኑት በመልክተኛው በሙሐመድ ﷺ ነው። እውነተኞች መሆናቸውን የሚያመለክቱ ታምራትና ምልክቶችን ለሁሉም የሰጣቸው ሲሆን፣ሁሉም ሰዎችን ከፈጣሪ ጌታቸው ጋር አስተዋውቀዋል፤የተሰጣቸውን ተልእኮም በታማኝነት ተወጥተዋል። በመሆኑም ከአላህ ተልከው ባደረሱት መልክትና በእውነታኛነታቸው ያላመነ ሰው በአላህ አላመነም። አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(ءَامَنَ ٱلرَّسُولُ بِمَآ أُنزِلَ إِلَيۡهِ مِن رَّبِّهِۦ وَٱلۡمُؤۡمِنُونَۚ كُلٌّ ءَامَنَ بِٱللَّهِ وَمَلَٰٓئِكَتِهِۦ وَكُتُبِهِۦ وَرُسُلِهِ)

‹‹መልክተኛው፣ከጌታው ወደርሱ በተወረደው አመነ፤ምእመኖችም (እንደዚሁ)፤ሁሉም በአላህ፣በመላእክቱም፣በመጻሕፍቱም፣በመልክተኞቹም፣ . . . አመኑ፤››

[አልበቀራህ፡258]

ከአላህﷻ የተላኩ በመሆናቸውም አንዳቸውን ከሌላው ሳንለይ በሁሉም እናምናለን። አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(لَا نُفَرِّقُ بَيۡنَ أَحَدٖ مِّن رُّسُلِهِ)

‹‹ከመልክተኞቹ በአንድም መካከል አንለይም፣(የሚሉ ሲኾኑ)፣››

[አልበቀራህ፡258]

አላህ ﷻ የሰው ልጆች የሚመሩባቸው ብርሃን ይሆኑ ዘንድ፣ከመልክተኞቹ ጋር መለኮታዊ መጽሐፎችን አውርዷል። በዚህም መሰረት ለኢብራሂም ሱሑፍን (ጽሑፎቹን)፣ለዳውድ ዘቡርን፣ለሙሳ ተውራትን፣ለለዒሳ ኢንጂልን፣ለሙሐመድ ﷺ ደግሞ ታምራዊውን ታላቁን ቁርኣን ሰጥቷል። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(كِتَٰبٌ أُحۡكِمَتۡ ءَايَٰتُهُۥ ثُمَّ فُصِّلَتۡ مِن لَّدُنۡ حَكِيمٍ خَبِيرٍ ١)

‹‹(ይህ ቁርኣን) አንቀጾቹ በጥንካሬ የተሰከኩ፣ከዚያም የተዘረዘሩ የኾነ መጽሐፍ ነው፤ጥበበኛ ውስጠ ዐዋቂ ከኾነው ዘንድ (የተወረደ) ነው።››

[ሁድ፡1]

አላህ ﷻ ቁርኣንን መመሪያ፣ብርሃን፣ብሩክና አስረጅ አድርጎታል። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(وَهَٰذَا كِتَٰبٌ أَنزَلۡنَٰهُ مُبَارَكٞ فَٱتَّبِعُوهُ وَٱتَّقُواْ لَعَلَّكُمۡ تُرۡحَمُونَ ١٥٥)

‹‹ይህም ያወረድነው የኾነ የተባረከ መጽሐፍ ነው፤ተከተሉትም፤ይታዘንላችሁም ዘንድ (ከክሕደት) ተጠንቀቁ።››

[አልአንዓም፡155]

በተጨማሪም አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(يَٰٓأَيُّهَا ٱلنَّاسُ قَدۡ جَآءَكُم بُرۡهَٰنٞ مِّن رَّبِّكُمۡ وَأَنزَلۡنَآ إِلَيۡكُمۡ نُورٗا مُّبِينٗا ١٧٤)

‹‹እላንተ ሰዎች ሆይ! ከጌታችሁ ዘንድ በእርግጥ አስረጅ መጣላችሁ፤ወደናንተም ገላጭ የኾነን ብርሃን (ቁርኣንን) አወረድን።››

[አልኒሳእ፡174]

አላህﷻ ከሰው ልጆች ሁሉ ተመራጭና የነቢዮችና የመልክተኞች መደመደሚያ በሆኑት ታላቁ ሙሐመድ ﷺ ማመንን፣ይዘው የመጡትን ትምሕርት አምኖ መቀበልን በአላህ አንድነት ከማመን ጋር የተቆራኘ አድርጎታል። የእስላም የመጀመሪያው ማእዘን የሆነው ‹‹አሽሀዱ አን ላ እላሀ እልለሏህ ወአሽሀዱ አንነ ሙሐመደን ረሱሉሏህ›› (ከአላህ በቀር ሌላ አምላክ አለመኖሩን እመሰክራለሁ፤ሙሐመድም የአላህ መልክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ) የሚለው ቃለ ተውሒድ (ሸሃዳ)፣በአላህ ማመንን ሙሐመድ አላህ መልክተኛ መሆናቸውን ከማመን ጋር አንድ ላይ ያጣመረ ቃለ ምስክርነት ነው። አላህﷻ ነቢዩን ለዓለማት ሁሉ እዝነትና ርህራሄ አድርጎ ልኳቸዋል። ነቢዩም ﷺ ሰዎችን ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ከማይምነት ወደ ዕውቀት፣ከጥመት ወደ ቅን መንገድና ወደ ኢማን አውጥተዋል። የተጣለባቸውን አደራም በሚገባ ተወጥተዋል፤ሕዝባቸውንም በፍጹምነት መክረዋል። ለሕዝባቸው እምነትም በጣም ሚጓጉ አሳቢ ነበሩ።

ይህን በማስመልከት አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(لَقَدۡ جَآءَكُمۡ رَسُولٞ مِّنۡ أَنفُسِكُمۡ عَزِيزٌ عَلَيۡهِ مَا عَنِتُّمۡ حَرِيصٌ عَلَيۡكُم بِٱلۡمُؤۡمِنِينَ رَءُوفٞ رَّحِيمٞ ١٢٨)

‹‹ከጎሳችሁ የኾነ፣ችግራችሁ በርሱ ላይ ጥኑ የኾነ፣በናንተ (እምነት) ላይ የሚጓጓ፣ለምእመናን ርኅሩህ አዛኝ የኾነ መልክተኛ፣በእርግጥ መጣላች።››

[አልተውባህ፡128]

አላህﷻ ለነቢዩና ለመልክተኛው ምእመናን ሊወጠዋቸው የሚገቡ ተገቢ ክብርና መብት ሰጥቷቸዋል፤የሰው ልጆች ምርጥና ተቀዳሚ መሪም አድርጓቸዋል። ይህን አስመልክተው ነቢዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል፦

‹‹እኔ ከኣደም ልጆች ሁሉ ተመራጩ መሪ ነኝ፤(በአላህ ባሪያነቴ እንጂ) በዚህ ግን አልፎክርም።››

(በእብን ማጀህ የተዘገበ)

ለነቢዩ ﷺ ካሉብን ኃላፊነቶች መካከል፦

1-

የአላህ ባሪያና መልክተኛው መሆናቸውን፣አላህﷻ ለዓለማት እዝነት አድርጎ የላካቸው፣አደራውን በታማኝነት ያደረሱና ተልእኮውን በተሟላ መልኩ የፈጸሙ መሆናቸውን ማመን ዋነኞቹ ናቸው። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(فَئامِنُواْ بِٱللَّهِ وَرَسُولِهِۦ وَٱلنُّورِ ٱلَّذِيٓ أَنزَلۡنَا)

‹‹በአላህና በመልክተኛውም፣በዚያም ባወረድነው ብርሃን እመኑ።››

[አልተጋቡን፡8]

ነቢዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል፦

‹‹የሙሐመድ ነፍስ በእጁ በሆነው (አላህ) እምላለሁ፤ከዚህ ሕዝብ (ኡመት) ውስጥ አይሁዳዊም ይሁን ክርስቲያን፣መልእክቴን ከሰማ በኋላ በተላክሁበት ነገር ሳያምን የሞተ ማንኛውም ሰው፣ከእሳት ጓዶች አንዱ ከመሆን ውጭ ሌላ ዕድል የለውም።››

(በሙስሊም የተዘገበ)

2-

ነቢዩﷺ ከጌታቸው ዘንድ ይዘው የመጡትን ሁሉ አምኖ መቀበል፣ከአላህ ያመጡት ሁሉ ያለ ምንም ጥርጣሬ ፍጹም እውነት መሆኑን በእርግጠኝነት ማመን። አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(إِنَّمَا ٱلۡمُؤۡمِنُونَ ٱلَّذِينَ ءَامَنُواْ بِٱللَّهِ وَرَسُولِهِۦ ثُمَّ لَمۡ يَرۡتَابُواْ)

‹‹(እውነተኞቹ) ምእምናን እነዚያ በአላህና በመልክተኛው ያመኑት፣ከዚያም ያልተጠራጠሩት፣ . . . ብቻ ናቸው፤››

[አልሑጁራት፡15]

በተጨማሪም ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(فَلَا وَرَبِّكَ لَا يُؤۡمِنُونَ حَتَّىٰ يُحَكِّمُوكَ فِيمَا شَجَرَ بَيۡنَهُمۡ ثُمَّ لَا يَجِدُواْ فِيٓ أَنفُسِهِمۡ حَرَجٗا مِّمَّا قَضَيۡتَ وَيُسَلِّمُواْ تَسۡلِيمٗا ٦٥)

‹‹በጌታህም እምላለሁ (አላህ በራሱ መማሉ ነው)፤በመካከላቸው በተከራከሩበት ፍርድ እስከሚያስፈርዱህ፣ከዚያም ከፈረድከው ነገር በነፍሶቻቸው ውስጥ ጭንቀትን እስከማያገኙና ፍጹም መታዘዝንም እስከሚታዘዙ ድረስ አያምኑም፣(ምእምን አይሆኑም)።››

[አልኒሳእ፡65]

3-

ነቢዩን ﷺ መውደድ። አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(قُلۡ إِن كَانَ ءَابَآؤُكُمۡ وَأَبۡنَآؤُكُمۡ وَإِخۡوَٰنُكُمۡ وَأَزۡوَٰجُكُمۡ وَعَشِيرَتُكُمۡ وَأَمۡوَٰلٌ ٱقۡتَرَفۡتُمُوهَا وَتِجَٰرَةٞ تَخۡشَوۡنَ كَسَادَهَا وَمَسَٰكِنُ تَرۡضَوۡنَهَآ أَحَبَّ إِلَيۡكُم مِّنَ ٱللَّهِ وَرَسُولِهِۦ وَجِهَادٖ فِي سَبِيلِهِۦ فَتَرَبَّصُواْ حَتَّىٰ يَأۡتِيَ ٱللَّهُ بِأَمۡرِهِۦۗ وَٱللَّهُ لَا يَهۡدِي ٱلۡقَوۡمَ ٱلۡفَٰسِقِينَ ٢٤ )

‹‹፦ አባቶቻችሁና ወንዶች ልጆቻችሁ፣ወንድሞቻችሁም፣የሰበሰባችኋቸው ሀብቶችም፣መክሰሩዋን የምትፈሩዋት ንግድም፣የምትወዷቸው መኖሪያዎችም፣እናንተ ዘንድ ከአላህና ከመልክተኛው፣በርሱ መንገድም ከመታገል፣ይበልጥ የተወደዱ እንደኾኑ፣አላህ ትእዛዙን እስኪያመጣ ድረስ ተጠባበቁ፣በላቸው፤አላህም አመጠኞች ሕዝቦችን አይመራም።››

[አልተውባህ፡24]

ነቢዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል፦

‹‹አንዳችሁ፣ከአባቱ ከልጁና ከሰዎች ሁሉ ይበልጥ እርሱ ዘንድ የተወደድኩ እስካልሆንኩ ድረስ፣(እውነተኛ) አማኝ አይሆንም።››

(በቡኻሪ የተዘገበ)

4-

ነቢዩን ﷺ ማክበርና ደረጃቸውን ማላቅ። አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(لِّتُؤۡمِنُواْ بِٱللَّهِ وَرَسُولِهِۦ وَتُعَزِّرُوهُ وَتُوَقِّرُوهُ)

‹‹በአላህ ልታምኑ፣በመልክተኛውም፣(ልታምኑ) ልትረዱትም ልታከብሩትም፣››

[አልፈትሕ፡9]

በተጨማሪም አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(فَٱلَّذِينَ ءَامَنُواْ بِهِۦ وَعَزَّرُوهُ وَنَصَرُوهُ وَٱتَّبَعُواْ ٱلنُّورَ ٱلَّذِيٓ أُنزِلَ مَعَهُۥٓ أُوْلَٰٓئِكَ هُمُ ٱلۡمُفۡلِحُونَ ١٥٧)

‹‹እነዚያም በርሱ ያመኑ፣ያከበሩትም፣የረዱትም፣ያንን ከርሱ ጋር የተወረደውን ብርሃን የተከተሉ፣እነዚያ እነሱ የሚድኑ ናቸው።››

[አልአዕራፍ፡157]

5-

ነቢዩን ﷺ ማፍቀርና መውደድ፣ሙስሊም ሆነው በርሳቸው መንገድ የተጓዙና ፈለጋቸውን የተከተሉ ቤተሰቦቻቸውን ማክበር፣ነቢያችን ሙሐመድ ﷺ ስለ ቤተሰቦቻቸው የሰጡትን ማሳሰቢያ መቀበል። ነቢዩﷺ እንዲህ ብለዋል፦

‹‹በቤተሰቦቼ ጉዳይ አላህን እንድታስቡ አስታውሳችኋለሁ፤በቤተሰቦቼ ጉዳይ አላህን እንድታስቡ አስታውሳችኋለሁ፤በቤተሰቦቼ ጉዳይ አላህን እንድታስቡ አስታውሳችኋለሁ።››

(በሙስሊም የተዘገበ)

የነቢዩﷺ ቤተሰብ የሚባሉት ባለቤቶቻቸውን፣ልጆቻቸውንና ዘካ መቀበል ሐራም የተደረገባቸውን የቅርብ ዘመዶቻቸውን የሚያካትት የክቡራን ሰዎች ስብስብ ነው። አህሉል በይትን ክብራቸውን መንካትና መዝለፍ የማይፈቀድ ሲሆን፣ከኃጢአት የተጠበቁና ከአላህ ሌላ የሚመለኩ አድርጎ መውሰድም የተከለከለ ነው።

6-

አምነው የተከተሏቸውን ባልደረቦቻቸውን (ሶሓባ) በክፉ አለማንሳት፣ታሪካቸውን አለማጉደፍና የነቢዩ ሶሓባ አላህ ﷻ ያሞገሳቸው ትውልድ መሆናቸውን ማወቅ። ይህን በማስመልከት አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

( مُّحَمَّدٞ رَّسُولُ ٱللَّهِۚ وَٱلَّذِينَ مَعَهُۥٓ أَشِدَّآءُ عَلَى ٱلۡكُفَّارِ رُحَمَآءُ بَيۡنَهُمۡۖ تَرَىٰهُمۡ رُكَّعٗا سُجَّدٗا يَبۡتَغُونَ فَضۡلٗا مِّنَ ٱللَّهِ وَرِضۡوَٰنٗاۖ سِيمَاهُمۡ فِي وُجُوهِهِم مِّنۡ أَثَرِ ٱلسُّجُودِ)

‹‹የአላህ መልክተኛ ሙሐመድ፣እነዚያም ከርሱ ጋር ያሉት (ወዳጆቹ) በከሐዲዎቹ ላይ ብርቱዎች፣በመካከላቸው አዛኞች ናቸው፤አጎንባሾች ሰጋጆች ኾነው ታያቸዋል፤ከአላህ ችሮታንና ውዴታን ይፈልጋሉ፤ምልክታቸው ከስግደታቸው ፈለግ ስትኾን በፊቶቻቸው ላይ ናት፤››

[አልፈትሕ፡29]

ስለ ሶሓባ ሲናገሩ ነቢዩﷺ እንዲህ ብለዋል፦

‹‹ባልደረቦቼን አትዝለፉ! ባልደረቦቼን አትዝለፉ! ነፍሴ በእጁ በሆነው እምላለሁ፣አንዳችሁ የኡሑድን ተራራ የሚያክል ወርቅ ቢለግስ እንኳ (ምንዳው) የነሱን አንድ እፍስም (ሙድ) ሆነ ግማሹንም እንኳ አይደርስም።››

(በሙስሊም የተዘገበ)

ከሶሓባ በደረጃ ባላጮቹ አራቱ ቅን ኸሊፋዎች ማለትም አቡ በክር፣ዑመር፣ዑሥማንና ዐሊይ (ረ.ዐ) ናቸው። አላህ ﷻ እንዲህ ብሏል፦

(وَٱلسَّٰبِقُونَ ٱلۡأَوَّلُونَ مِنَ ٱلۡمُهَٰجِرِينَ وَٱلۡأَنصَارِ وَٱلَّذِينَ ٱتَّبَعُوهُم بِإِحۡسَٰنٖ رَّضِيَ ٱللَّهُ عَنۡهُمۡ وَرَضُواْ عَنۡهُ وَأَعَدَّ لَهُمۡ جَنَّٰتٖ تَجۡرِي تَحۡتَهَا ٱلۡأَنۡهَٰرُ خَٰلِدِينَ فِيهَآ أَبَدٗاۚ ذَٰلِكَ ٱلۡفَوۡزُ ٱلۡعَظِيمُ ١٠٠)

‹‹ከስደተኞቹና ከረዳቶቹም ሲኾኑ፣የመጀመሪዎቹ ቀዳሚዎች፣እነዚያም በበጎ ሥራ የተከተሏቸው፣አላህ ከነሱ ወዷል (ሥራቸውን ተቀብሏል)፤ከርሱም ወደዋል (በተሰጣቸው ምንዳ ተደስተዋል)፤በሥሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸን፣ገነቶች በውስጣቸው ዘለዓለም ነዋሪዎች ሲኾኑ ለነርሱ አዘጋጅቶላቸዋል፣ይህ ታላቅ ዕድል ነው።››

[አልተውባህ፡100]

የነቢዩ ﷺ ባልደረቦች ከነቢዩ የተቀበሉትን ለኛ ያደረሱና የጠራ ሃይማኖትና ዕውቀት ያስተላለፉልን የወርቃማው ትውልድ አባላት ናቸው።



Tags: