የጌታ (አርረብ) ትርጉም፦

የጌታ (አርረብ) ትርጉም፦

ጌታው (አልርረብ)፦ አቻ የሌለው መሪ አለቃ፣በዘረጋላቸው ጸጋው አማካይነት የፍጥረታቱን ጉዳይ የሚያበጅ፣መፍጠርና ማዘዝ የርሱ ብቻ የሆነ ገዥ ማለት ነው። ጌታ የሚለው ቃል የ --- ጌታ፣ለምሳሌ የቤቱ ጌታ፣የንብረቱ ጌታ . . ተብሎ ከቅጥያ ጋር እንጂ ፍጡራንን በተመለከተ አገልግሎት ላይ አይውልም። ያለ ቅጥያ የሚያገለግለው ለአላህ ﷻ ብቻ ነው።

ሰዎች የሚያመልኩት አምላክ (እላህ) እንደሚስፈልጋቸው ከማወቃቸው በፊት፣ጌታ እንደሚያስፈልጋቸው የሚያወቁ፣ከወደፊት ጉዳዮቻቸው በፊት የአሁን ችግራቸው እንዲፈታላቸው የሚፈልጉ እንደ መሆናቸው፣የአላህን ጌትነት (ሩቡብያህ) መቀበላቸው አምላክነቱን (ኡሉህይያን)፣አምልኮቱን፣ከርሱ ረድኤት መለመንን፣በርሱ ላይ መመካትን፣ወደርሱ መማለስን . . አምኖ ከመቀበላቸው የሚቀድም ሆኗል።

ጌታና ጌትነት ታላላቅ ትርጉሞችን የያዙ ሲሆን፣ከነዚህም የፍጹማዊ ሥልጣን ባለቤትነትን፣ሲሳይና ጤናን፣እንዲሁም ስኬትንና መመሪያ መስጠትን የመሳሰሉ ይገኙባቸዋል። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

( وَٱلَّذِي هُوَ يُطۡعِمُنِي وَيَسۡقِينِ ٧٩ َإِذَا مَرِضۡتُ فَهُوَ يَشۡفِينِ ٨٠ وَٱلَّذِي يُمِيتُنِي ثُمَّ يُحۡيِينِ ٨١)

‹‹ያም እርሱ የሚያበላኝና የሚያጠጣኝ ነው። በታመምኩም ጊዜ፣እርሱ ያሽረኛል። ያም የሚገድለኝ፣ከዚያም ሕያው የሚያደርገኝ ነው።››

[አልሹዐራ፡79-81]

ፍጥረታትን ሁሉ የፈጠረ፣በጥበቡ ሰርቶ ያስተካከለ፣በቸርነቱና በዕውቀቱ ያሳመረ፣እርሱ አላህ ﷻ ፈጣሪው፣ከኢምንት አስገኚው፣ቅርጽን አሳማሪው ነው። ሁሌና ምንጊዜም በዚህ ታላቅ ባሕርይ የሚገለጽ ነው።

ጌታው አላህ፦ በማቀናበርና በጸጋዎቹ ዓይነቶች ሁሉንም አገልጋዮቹን የሚያንጽ ሲሆን፣እነጻው ልቦናቸውን፣መንፈሳቸውንና ስነምግባራቸውን በማበጀት ረገድ ለምርጥ ወዳጆቹ የተለየ ነው። ምርጥ ባሮቹ ይህን ልዩ እነጻ ከርሱ ስለሚፈልጉ፣በዚህ ክቡር ስሙ እርሱን አብዝተው ይጠሩታል፤ ይለምኑታል።



Tags: