ክፍል አንድ - ዕባዳዎች በልብ ላይ የሚያሳርፉት አሻራ(መውደድ ፦)

ክፍል አንድ - ዕባዳዎች በልብ ላይ የሚያሳርፉት አሻራ(መውደድ ፦)
1) መውደድ ፦

የመውደድ ጽንሰ ሀሳብ ፦

የአላህ ውዴታ፦

አላህንﷻ መውደድና እርሱን ማፍቀር ማለት የልብ በርሱ መጽናናትና ወደርሱ ማዘንበል፣እርሱ ለሚፈልገው ነገር ሁሉ ምላሽ መስጠት፣የርሱ ውዳሴና ዝክር ልብን መቆጣጠር ማለት ነው።

የአላህ ፍቅር እውነታ

አላህን ማፍቀር ዕባዳውን ማፍቀር፣ለርሱ መተናነስና እርሱን ማላቅ ነው። ይህም በአፍቃሪው ልብ ውስጥ ትእዛዛቱን በመፈጸምና ከእገዳዎቹ በመታቀብ የሚገለጽ የተፈቃሪው አላህﷻ አክብሮትና ልቅና መኖር ማለት ነው። ይህ ፍቅር የኢማንና የተውሒድ መሠረት ሲሆን፣የሚያስገኘው የትሩፋት ውጤቶች ከቁጥር በላይ ናቸው። አላህ የሚወዳቸውን ቦታዎች፣ጊዜያትና ግለሰቦች፣አካላዊና አንደበታዊ ተግባራትንና የመሳሰሉትን አላህ የሚወዳቸውን ነገሮች ሁሉ መውደድም አላህንﷻ የመውድና የማፍቀር አካል ነው።

የአላህ ፍቅር ለርሱ ብቻ ፍጹም የተደረገ መሆን ሲኖርበት፣ተፈጥሯዊ የሆነ ወላጆችን ልጆችን መምህርን፣ምግብና መጠጥን፣ትዳራዊ ግንኑነትን፣አልባሳትን ወዳጆችንና የመሳሰሉትን ከመውደድና ከማፍቀር ጋር አይጋጭም።

ሐራም ሆኖ የተከለከለው ፍቅር፣ሙሽሪኮች ጣዖቶቻቸውንና አማልክቶቻቸውን አላህን እንደሚወዱ መውደድ፣ነፍስያ የምትወዳቸውን ነገሮች ፍቅር ከአላህﷻ ፍቅር ማብለጥ ወይም አላህ ﷻ የማይወዳቸውን ጊዜያትና ቦታዎችን፣ግለሰቦችን፣ሥራዎችን፣ንግግሮችን መውደድ ነው። አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(وَمِنَ النَّاسِ مَنْ يَتَّخِذُ مِنْ دُونِ اللَّهِ أَنْدَادًا يُحِبُّونَهُمْ كَحُبِّ اللَّهِ وَالَّذِينَ آَمَنُوا أَشَدُّ

حُبًّا لِلَّهِ)

‹ከሰዎችም ከአላህ ሌላ ባላንጣዎችን (ጣዖታትን)፣አላህን እንደሚወዱ የሚወዷቸው ኾነው የሚይዙ አልሉ፤እነዚያ ያመኑትም፣አላህን በመውደድ (ከነርሱ) ይበልጥ የበረቱ ናቸው፤››

[አልበቀራህ፡165]

ከአላህ ፍቅር ትሩፋቶች መካከል ፦

1-

የተውሒድ መሰረትና የተውሒድ መንፈስ መሆኑ፣ፍቅርና ውዴታን ለአላህ ብቻ ፍጹም ማድረግ ነው። ይህ የዕባዳ መሰረታዊ እውነታ ነው። አንድ አማኝ ለአላህ ያለው ፍቅር የተሟላ እስኪሆንና ከሚወዳቸው ነገሮች ሁሉ ቀዳሚ፣የተቀሩት ተፈቃሪዎቹ ለዚህ የተድላውና የመድህኑ መገኛ ለሆነው ዐቢይ ፍቅር ተመሪ በሚሆኑበት ሁኔታ የአላህﷻ ፍቅር የበላይ ተቆጣጣሪና ወሳኝ እስኪሆን ድረስም ተውሒድ ምሉእ አይሆንም።

2-

የአላህ አፍቃሪ በችግርና በመከራ ወቅት መጽናኛ የሚያገኝ መሆኑ። አፍቃሪ ችግሮችን የሚያስረሳና መከራዎችን የሚያዘናጋው የፍቅር ጣዕምና ስሜት ይሰማዋል።

አላህﷻ ከሚመለክባቸው ዕባዳዎች ሁሉ፣ፍቅርን ፍርሃትንና ተስፋ በርሱ ላይ መጣልን ከመሳሰሉት የዕባዳ ዓይነቶች የሚበልጡ የሉም።

አላህን ለመገናኘት መናፈቅና መጓጓት፣የዓለማዊ ሕይወት ጣጣዎችን ከልብ የሚያባርር የሕይወት መንፈስ ነው።

3-

የተሟላ ደስታና ምቾት ፦ ይህ ሊገኝ የሚችለው አላህን ﷻ በማፍቀር ብቻ ነው። ልብ ከብቸኝነቱ የሚወጣው፣የፍቅር ረሃቡንና ጥማቱን የሚያረካው በአላህ ፍቅርና ወደርሱ ብቻ በመመለስ ነው። ሁሉም ቁሳዊ ደስታዎችና መደሰቻዎች ቢሟሉለት እንኳ በአላህ ﷻ ፍቅርና በርሱ ውዴታ ብቻ እንጂ ልብ መጽናናትና መረጋጋት አይችልም። የርሱ ፍቅር የሕሊና ደሰታና የመንፈስ እርካታ ነው። ጤናማ ልቦችና በጎ መንፈስ፣የጠራ ሕሊና እና የጸዳ ልቦና ባላቸው ሰዎች ዘንድ ከርሱ ፍቅር ይበልጥ የሚጣፍጥ፣የሚያዝናና የሚያጽናና፣የርሱን ግንኑነት ከመናፈቅ ይበልጥ የሚያረካ ምንም ነገር የለም። በአንድ ሙእምን ልብ ውስጥ ያለው የኢማን ጣእምና ጥፍጥናው ከምንም በላይ ነው። የሚሰማው ደስታና እርካታም ከየትኛውም ደስታና እርካታ ይበልጥ የተሟላ ነው።

‹‹ሦስት ነገሮች ያሉት ሰው የኢማንን ጥፍጥና ያገኝባቸዋል ፦ አላህና መልክተኛው ከተቀሩት ሁሉ እርሱ ዘንድ ይበልጥ የተወደዱ መሆን፤ለአላህ ብሎ ብቻ አንድን ሰው የሚወድ መሆን፤አላህ አንዴ ከርሱ ካዳነው በኋላ ወደ ኩፍር መመለስን ወደ እሳት መወርወርን የሚጠላውን ያህል የሚጠላ መሆን ናቸው።››

(በቡኻሪ፣በሙስሊምና በነሳኢ የተዘገበ)

በአላህ ﷻ ፍቅር መርካታን፣በርሱ መረጋጋትንና በርሱም መጽናናትን ከተነፈገ ሰው ይበልጥ በምድረ ዓለም ላይ ዕድለቢስ የሆነ መናጢ የለም።

የአላህን ፍቅር የሚያስገኙ ምክንያቶች ፦

ጌታችን ﷻ የሚወዱትን ይወዳቸዋል፣ የሚቀርቡትንም ይቀርባቸዋል። የአላህን ፍቅር የሚያስገኘው የመጀመሪያው ምክንያት ባሪያው፣ከፍጥረታቱ ውስጥ ማንንምና ምንንም በማይወድ ውዴታ ፈጣሪ ጌታውን መውደድ ነው። የአላህን ውዴታ የሚያስገኙ ዝርዝር ምክንያቶች የሚከተሉት ናቸው ፦

1-

ቁርኣንን ትርጉሙንና መልክቱን እያስተነተኑ በአስተውሎና በግንዛቤ ማንበብ። ራሱን በአላህ መጽሐፍ የጠመደና ጥናቱን ሥራዬ ብሎ የያዘ ሰው፣ልቡ በአላህ ፍቅር የታነጸና የተሞላ ይሆናል።

2-

መደበኛ ግዴታዎችን ከፈጸሙ በኋላ ተጨማሪ በሆኑ የሱንና ዕባዳዎች (ነዋፍል) ወደ አላህ መቃረብ።

‹‹ባሪያዬ እኔ እስክወደው ግዴታ ባልሆኑ ተጨማሪ የሱንና ሥራዎች (ነዋፍል) በመፈጸም ወደ እኔ ይቃረባል። በወደድኩት ጊዜ የሚሰማበት ጆሮው፣የሚያይበት ዓይኑ፣የሚይዝበት እጁና የሚጓዝበት እግሩ እሆንለታለሁ። ከለመነኝ በእርግጥ እሰጠዋለሁ። ከክፉ ነገር የኔን ጥበቃ ከለመነኝም በእርግጥ እጠብቀዋለሁ።››

(በቡኻሪ የተዘገበ ሐዲሥ አልቁድሲ)

3-

በሁሉም ሁኔታዎች በአንደበትና በልብ፣ በተግባርና በስነምግባር አላህን ﷻ ማውሳትና የርሱን ዝክር ማዘውተር።

4-

አላህ የሚወዳቸውን ነገሮች፣ነፍስያ ከምትወዳቸው ፍላጎቶችና ቁሳዊ መደሰቻዎች ማስቀደም።

(يُحِبُّهُمۡ وَيُحِبُّونَهُ )

‹‹የሚወዳቸውንና የሚወዱትን።››

[አልማኢዳህ፡54]

5-

ልብን የአላህን ﷻ ስሞችና ባህርያት እንዲያጠና እና እንዲያውቅ ማድረግ።

6-

ውለታዎቹን፣ጸጋዎቹን፣ግልጽና ስውር ችሮታዎቹን ማስተዋል።

7-

የልብ አላህ ﷻ ፊት ሙሉ በሙሉ መተናነስና መሰባበር።

8-

ጌታችን ﷻ ወደ ቅርቢቱ ሰማይ በሚወርድበት የሌሊት የመጨረሻው ሲሦ፣ በዱዓእ፣በዝክርና ቁርኣንን በማንበብ፣በተሟላ አደብ ከፊቱ ቆሞ በመስገድ፣ከዚያም ምህረቱን በመለመን በተውበትና በእስትግፋር በማጠናቀቅ ከአላህ ጋር መሆን።

9-

ከእውነተኛ የአላህ ወዳጆች ጋር መቀመጥ፣ መልካም የአዝመራ ፍሬ እንደሚለቀመው የንግግራቸውን መልካም ፍሬዎች መልቀምና መሰብሰብ። መናገር ለራስና ለሌላውም ተጨማሪ ጠቃሜታ ያለው ሆኖ እስካልተገኘ ድረስ በዝምታ መቆየት።

10-

ልብን ከአላህ ﷻ ከሚለዩ ምክንያቶች ሁሉ መራቅና ምክንያቶቹንም ማራቅ።

የአላህ ፍቅር ለባሪያው ከሚያስገኛቸው ጥቅሞች መካከል የሚከተሉትን እናገኛለን፦

- አላህ ﷻ የወደደውን ሰው ይመራል፣ ያቀርበዋል። ነቢዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹አላህን ﷻ እንዲህ ይላል ፦ እኔ ባሪያዬ ባሰበኝበት እገኛለሁ። እኔን ሲያስበኝ ከርሱ ጋር እገኛለሁ። በውስጡ ሲያስታውሰኝ በውስጤ አስታውሰዋለሁ። በጉባኤ ሲያስታውሰኝ ከርሱ ጉባኤ በላጭ በሆነ ጉባኤ ላይ አስታውሰዋለሁ። አንድ ስንዝር ወደኔ ከቀረበ በአንድ ክንድ ወደርሱ እቀርባለሁ። በአንድ ክንድ ወደኔ ከቀረበ በአንድ ባዕ (ሁለት እጆች ወደ ጎን ሲዘረጉ ከአንዱ መዳፍ እስከ ሌላኛው መዳፍ ለው ርቀት) ወደርሱ እቀርባለሁ። እየተራመደ ወደኔ ከመጣ እየሮጥኩ ወርሱ እመጣለሁ።››

(በቡኻሪ የተዘገበ)

ባሪያው ጌታውን በፈራና በተጠነቀቀ ቁጥር ወደ ሌላ መመሪያ ከፍ ይደረጋል። አላህን በወደደ ቁጥርም መመራት (ህዳያ) ይጨመርለታል። መመራት በተጨመረለት ቁጥርም ፍርሃትና ተቅዋ ይጨመርለታል።

- አላህ የወደደውን ሰው በምድር ላይ ተቀባይነት እንዲያገኝ ያደርጋል ፦

ተቀባይነት ያገኛል ማለት ጌታው የወደደው ይህ ባሪያ፣በሌሎች ዘንድ ውዴታና መልካም ዝና ያገኛል፣የአላህን ﷻ ውዴታ እምቢ ያለ በመሆኑ ካፍር ብቻ ሲቀር ሁሉም ነገር ይወደዋል፣ወደርሱ ያዘነብላል ማለት ነው። ረሱል ﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹አላህ አንድ አገልጋዩን ሲወደው ጅብሪልን ይጠራና፦ ‹እኔ እገሌን ወድጄዋለሁና አንተም ውደደው› ይላል። ጂብሪልም ይወደዋል፤ከዚያም ለሰማይ ነዋሪዎች፦ ‹አላህ እገሌን ይወደዋልና እናንተም ውደዱት› በማለት ያውጃል፤የሰማይ ነዋሪዎችም ይወዱታል፤በምድር ላይም ተቀባይነት እንዲኖረው ይደረጋል።››

(በሙስሊም የተዘገበ)

አላህ ﷻ አንድ ባሪያውን ሲወደው በዚህ መልኩ በጥበቃውና በእንክብካቤው ውስጥ አድርጎት፣ነገሮች ሁሉ በትእዛዙ ስር እንዲሆኑ ያደርግለታል። አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ገር ያደርግለታል። የራቀውን ሁሉ ያቀርብለታል። የዱንያን ጉዳይ ቀላል ያደርግለታል። ጭንቀትም ሆነ ልፋት አይሰማውም። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(إِنَّ ٱلَّذِينَ ءَامَنُواْ وَعَمِلُواْ ٱلصَّٰلِحَٰتِ سَيَجۡعَلُ لَهُمُ ٱلرَّحۡمَٰنُ وُدّٗا ٩٦)

‹‹እነዚያ ያመኑና በጎ ሥራዎችን የሠሩ፣ አልረሕማን ለነሱ ውዴታን ይሰጣቸዋል።››

[መርየም:96]

- አላህ የደደውን ሰው በራሱ አብሮነት ውስጥ ያደርገዋል ፦ አላህ ﷻ ባሪያውን ከወደደው በጥበቃውና በእንክብካቤው ከርሱ ጋር ይሆናል። ለሚጎዳውና ለሚያውከው ሰው አሳልፎ አይሰጠውም። ከጌታቸው በሚተላለፍላቸው ሐዲሥ አልቁድሲ ውስጥ ነቢዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹አላህ እንዲህ ብሏል ፦ የኔን ወዳጅ ጠላቱ ባደረገ ሰው ላይ ጦርነት አውጄበታለሁ፤ባሪያዬ እኔ እስክወደው ግዴታ ያልሆኑ ተጨማሪ የሱንና ሥራዎችን በመፈጸም ወደኔ ይቃረባል። በወደድኩት ጊዜ የሚሰማበት ጆሮው፣የሚያይበት ዓይኑ፣የሚይዝበት እጁና የሚጓዝበት እግሩ እሆንለታለሁ። ከለመነኝ በእርግጥ እሰጠዋለሁ። ከክፉ ነገር ለመዳን የኔን ጥበቃ ከለመነኝም በእርግጥ እጠብቀዋለሁ። ማድረጌ በማይቀረው ነገር ላይ፣እርሱ ሞትን የሚጠላ ሆኖ እኔ ደግሞ እርሱን ማስከፋት የምጣላ በመሆኔ የአማኝ ሰው ነፍስን ከመውሰድ ይበልጥ የማመነታበት ሌላ ምንም ነገር የለም።››

(በቡኻሪ የተዘገበ)

በአላህ መካድ ከሞት በፊት ሞትና የሐዘን መንስኤ እንደሆነ ሁሉ፣እውነተኛ ኢማን የነፍስ ሕይወት፣የደስተኝነትና የመታደል መገኛ ነው።

- አላህ የደደውን ሰው ጸሎቱን ይሰማለታል፤ የለመነውን ይሞላለታል። አላህ ﷻ ምእመናን ባሮቹን ለመውደዱ አንዱ ማስረጃ ገና እጆቻቸውን ወደ ሰማይ ከፍ አድርገው ‹‹ጌታዬ! ጌታዬ!›› ሲሉ በችሮታውና በቸርነቱ ጸሎታቸውን የሚቀበልላቸው መሆኑ ነው። አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(وَإِذَا سَأَلَكَ عِبَادِي عَنِّي فَإِنِّي قَرِيبٌۖ أُجِيبُ دَعۡوَةَ ٱلدَّاعِ إِذَا دَعَانِۖ فَلۡيَسۡتَجِيبُواْ لِي وَلۡيُؤۡمِنُواْ بِي لَعَلَّهُمۡ يَرۡشُدُونَ ١٨٦)

‹‹ባሮቼም ከኔ በጠየቁህ ጊዜ፣(እንዲህ በላቸው)፦ እኔ ቅርብ ነኝ፤የለማኝን ጸሎት በለመነኝ ጊዜ እቀበለዋለሁ፤ስለዚህ ለኔ ይታዘዙ፤በኔም ይመኑ፤እነርሱ ሊመሩ ይከጀላልና።››

[አልበቀራህ፡186]

ከሰልማን አልፋሪሲ በተላለፈው መሰረት የአላህ መልክተኛﷺ እንዲህ ብለዋል፦

‹‹አላህ ባለ ይሉኝታ ቸር ጌታ ነው፤አንድ ባሪያው እጆቹን ወደ ላይ ከፍ አድርጎ ሲለምነው ባዶ መመለስ ያሳፍረዋል።››

(በትርምዚ የተዘገበ)

አላህ አንድን ባሪያ ከደደው መላእኮች ምሕረት እንዲለምኑለትና እስትግፋር እንዲያደርጉለት ያደርጋል። መላእኮች አላህን ለሚወድ ሰው ከአላህ ምሕረትና እዝነቱን ይለምኑለታል።

አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(ٱلَّذِينَ يَحۡمِلُونَ ٱلۡعَرۡشَ وَمَنۡ حَوۡلَهُۥ يُسَبِّحُونَ بِحَمۡدِ رَبِّهِمۡ وَيُؤۡمِنُونَ بِهِۦ وَيَسۡتَغۡفِرُونَ لِلَّذِينَ ءَامَنُواْۖ رَبَّنَا وَسِعۡتَ كُلَّ شَيۡءٖ رَّحۡمَةٗ وَعِلۡمٗا فَٱغۡفِرۡ لِلَّذِينَ تَابُواْ وَٱتَّبَعُواْ سَبِيلَكَ وَقِهِمۡ عَذَابَ ٱلۡجَحِيمِ ٧)

‹‹እነዚያ ዐርሹን የሚሸከሙት፣እነዚያም በዙሪያው ያሉት፣በጌታቸው ምስጋና ያወድሳሉ፤በርሱም ያምናሉ፤ጌታችን ሆይ! ነገሩን ሁሉ በእዝነትና በዕውቀት ከበሃል፤ስለዚህ ለነዚያ ለተጸጸቱት፣መንገድህንም ለተከተሉት ምሕረት አድርግላቸው፤የእሳትንም ቅጣት ጠብቃቸው፣እያሉ ለነዚያ ላመኑት ምሕረትን ይለምናሉ።››

[አልሙእሚን፡7]

በተጨማሪም አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(تَكَادُ ٱلسَّمَٰوَٰتُ يَتَفَطَّرۡنَ مِن فَوۡقِهِنَّۚ وَٱلۡمَلَٰٓئِكَةُ يُسَبِّحُونَ بِحَمۡدِ رَبِّهِمۡ وَيَسۡتَغۡفِرُونَ لِمَن فِي ٱلۡأَرۡضِۗ أَلَآ إِنَّ ٱللَّهَ هُوَ ٱلۡغَفُورُ ٱلرَّحِيمُ ٥

‹‹(ከአላህ ፍራቻ) ሰማያት ከበላያቸው ሊቀደዱ ይቀርባሉ፤መላእክትም ጌታቸውን እያመሰገኑ ያወድሳሉ፤በምድርም ላለው ፍጡር ምሕረትን ይለምናሉ፤ንቁ አላህ እርሱ መሓሪው አዛኙ ነው።››

[አልሹራ፡5]

አላህ ﷻ አንድን ባሪያ ከወደደው በመልካም ሥራ ላይ እያለ ይገድለዋል። ረሱል ﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹አላህ ﷻ ለአንድ ባሪያው በጎውን ከሻለት ዝነኛ ተወዳጅ ያደርገዋል፤ዝነኛ ተወዳጅ መሆን ምን ማለት ነው?! ሲባሉ ከመሞቱ በፊት አላህ ﷻ የበጎ ሥራን በር ይከፍትለትና በዚያ ላይ እያለ እንዲሞት ያደርገዋል፣አሉ።››

(በአሕመድ የተዘገበ)

አላህ ﷻ ባሪያውን ከደደው በሚሞትበት ጊዜ መረጋጋትን ይሰጠዋል ፦

አላህﷻ አንድን ባሪያ ከደደው በቅርቢቱ የዱንያ ሕይወት ጸጥታና መረጋጋትን፣በሚሞትበት ጊዜም እርጋታና ጽናትን ያድለዋል። ነፍሱን በጥንቃቄና በዝግታ የሚያወጡ፣ነፍሱ ስትወጣ የሚያረጋጉት፣በጀነት በማብሰር የሚያጽናኑት መላእክትን ይልክለታል። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(إِنَّ ٱلَّذِينَ قَالُواْ رَبُّنَا ٱللَّهُ ثُمَّ ٱسۡتَقَٰمُواْ تَتَنَزَّلُ عَلَيۡهِمُ ٱلۡمَلَٰٓئِكَةُ أَلَّا تَخَافُواْ وَلَا تَحۡزَنُواْ وَأَبۡشِرُواْ بِٱلۡجَنَّةِ ٱلَّتِي كُنتُمۡ تُوعَدُونَ ٣٠)

‹‹እነዚያ ጌታችን አላህ ነው ያሉ፣ከዚያም ቀጥ ያሉ፦ አትፍሩ፤አትዘኑም፤በዚያችም ተስፋ ቃል ትደረግላችሁ በነበራችሁት ገነት ተበሰሩ፤በማለት በነሱ ላይ መላእክት ይወርዳሉ።››

[ሓ ሚም አልሰጅዳህ፡30]

አላህ ﷻ አንድን ባሪያ ከደደው ጀነት ውስጥ ለዘለዓለም ነዋሪ ያደርገዋል ፦

አላህ የደደው ሰው፣በወዲያኛው የኣኽራ ሕይወት በርሱ ጀነት ውስጥ ይሆናል። እዚያ የተደገሰለት ታላቅ መስተንግዶ በማንም አእምሮ ታስቦ የማያውቅ ድሎትና ምችት፣ነፍስ የምትፈልገው ሁሉ ያለ ገደብ የምታገኝበት፣ በቃላት የማይገለጽ ተድላ ነው። ቀጥሎ ባለው ሐዲሥ አልቁድሲ እንደተገለጸው ነቢዩ ﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹አላህ፦ ለደጋግ ባሮቼ ዓይን አይቶት የማያውቀውን፣ጆሮም ሰምቶት የማያውቀውንና በሰው ልጅ አእምሮ ውስጥ ታስቦ የማያውቀውን (ድሎት) አዘጋጅቻለሁ፣ብሏል።›› ከፈለጋችሁ፦

(فَلَا تَعۡلَمُ نَفۡسٞ مَّآ أُخۡفِيَ لَهُم مِّن قُرَّةِ أَعۡيُنٖ)

‹‹ከዓይኖች መርጊያ ለነሱ የተደበቀላቸውን (ጸጋ)፣ማንኛይቱም ነፍስ አታውቅም።›› የሚለውን አንብቡ።

(በቡኻሪ የተዘገበ)

የዱንያ ሕይወት የርሱ ﷻ ፍቅርና ለርሱ መታዘዝ ባይኖር ኖሮ፣በጀነትም እርሱን ማየትና መመልከት ባይኖር ኖሮ ባልጣሙ ነበር።

የአላህ ፍቅር ለባሪያው ከሚያስገኛቸው ፍሬዎች መካከል አንዱ እርሱን ﷻ መመልከት ነው ፦

ኃያሉ ጌታ አላህ ﷻ ለሚወዳቸው ባሮቹ በብርሃኑ ይገለጥላቸውና ያዩታል። ከዚያ ይበልጥ የሚወደድ ነገር ፈጽሞ አያዩም። ይህም ነቢዩ ﷺ አንድ ሌሊት ሙሉ ጨረቃን ተመልክተው በተናገሩት ሐዲሥ መሰረት ነው፦

‹‹ይህን ጨረቃ እንደምታዩ ጌታችሁን (በኣኽራ) ታዩታላችሁ፤በማየቱም ላይ መጨናነቅ አይኖርም። ፀሐይ ከመውጣቷና ከመጥለቋ በፊት ከመሰገድ አለመታከት ከቻላችሁ አድርጉ፣ብለው ፦

(وَسَبِّحۡ بِحَمۡدِ رَبِّكَ قَبۡلَ طُلُوعِ ٱلشَّمۡسِ وَقَبۡلَ ٱلۡغُرُوبِ ٣٩)”

‹‹ጌታህንም ከማመስገን ጋር ፀሐይ ከመውጣቷ በፊት፣ከመግባቷም በፊት አወድሰው።›› የሚለውን አነበቡ።

(በቡኻሪ የተዘገበ)

የአላህን ፍቅር የሚመለከቱ ብያኔዎችና ማሳሰቢያዎች፦

1-

አላህ ﷻ ባሪያውን መውደዱ መከራና ፈተናን ከርሱ አይከላከልም። የአላህ መልክተኛﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹የሽልማትና የምንዳ ክብደትት እንደ ፈተናው ክብደትና ግዝፈት ነው። አላህ ሰዎችን ሲወዳቸው በፈተና ይሞክራቸዋል። ወዶ የተቀበለ ውዴታውን ያገኛል፤የጠላውም ጥላቻውን ያተርፋል።››

(በትርምዚ የተዘገበ)

ከኃጢአት እስኪያጸዳውና ልቡ በዱንያ ከመጠመድ ነጻ እስኪሆን ድረስ አላህ ﷻ ባሪያውን በመከራዎች ይፈትነዋል። አላህﷻ እንዲህ ብሏል፦

(وَلَنَبۡلُوَنَّكُمۡ حَتَّىٰ نَعۡلَمَ ٱلۡمُجَٰهِدِينَ مِنكُمۡ وَٱلصَّٰبِرِينَ وَنَبۡلُوَاْ أَخۡبَارَكُمۡ ٣١)

‹‹ከናንተም ታጋዮችንና ታጋሾቹን እስከምናውቅ፣ወሬዎቻችሁንም እስከምንገልጽ ድረስ በእርግጥ እንሞክራችኋለን።››

[ሙሐመድ፡31]

በተጨማሪም አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(وَلَنَبۡلُوَنَّكُم بِشَيۡءٖ مِّنَ ٱلۡخَوۡفِ وَٱلۡجُوعِ وَنَقۡصٖ مِّنَ ٱلۡأَمۡوَٰلِ وَٱلۡأَنفُسِ وَٱلثَّمَرَٰتِۗ وَبَشِّرِ ٱلصَّٰبِرِينَ ١٥٥ ٱلَّذِينَ إِذَآ أَصَٰبَتۡهُم مُّصِيبَةٞ قَالُوٓاْ إِنَّا لِلَّهِ وَإِنَّآ إِلَيۡهِ رَٰجِعُونَ ١٥٦ أُوْلَٰٓئِكَ عَلَيۡهِمۡ صَلَوَٰتٞ مِّن رَّبِّهِمۡ وَرَحۡمَةٞۖ وَأُوْلَٰٓئِكَ هُمُ ٱلۡمُهۡتَدُونَ ١٥٧)

‹ከፍርሃትና ከረኃብምም በጥቂት ነገር፣ከገንዘቦችና ከነፍሶችም ከፍራፍሬዎችም በመቀነስ በእርግጥ እንሞክራችኋለን፣ታጋሾችንም (በገነት) አብስር።››

[አልበቀራህ፡155-157]

2-

ባሪያው የጌታውንﷻ ትእዛዝ ሲጥስ ለአላህ ያለው ውዴታ ይቀንሳል፤ኃጢአቱ ፍቅሩን ጎደሎ ያደርጋል። የአላህ ፍቅር እንደ ኢማን ሁሉ መነሻ መሰረትና ሙላት ያለው ሲሆን፣ምሉእነቱ እንደ ኃጢአቱ ሁኔታ ይቀንሳል። ግለሰቡ ወደ ጥርጣሬና መናፍቅነት ደረጃ ከወረደ፣ስረ መሰረቱ ተነቅሎ ይጠፋል። ልቡ ውስጥ ምንም የአላህ ፍቅር የሌለው ሰው ተቀልባሽ ከሓዲና ከሃይማኖቱ እጣ ፈንታ የሌለው መናፊቅ ነው። ኃጢአን ግን የአላህﷻ ፍቅር በውስጣቸው የለም ማለት አይቻልም፤ለአላህ ያላቸው ፍቅር ጎደሎ ነው ተብለው በዚህ መሰረት ይፈረጃሉ። ነቢዩﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹እናንተ ኃጢአት የማትሠሩ ብትኾኑ ኖሮ፣አላህ ﷻ ኃጢአት የሚሠሩና ምሕረት የሚያደርግላቸውን ሰዎች በፈጠረ ነበር።››

(በአሕመድ የተዘገበ)

‹‹ነጻነት ማለት የልብ ከሽርክ፣ከስሜታዊ ዝንባሌዎችና ከውዥንብሮች ነጻ መሆን ነው። ተገዥነትና ባርነት ደግሞ የልብ ለአንድ አላህ ብቻ ተገዥና ታዛዥ መሆንና ለሌላ ለማንምና ለምንም ተገዥ አለመሆን ነው።››

3-

አላህን መውደድ የሰው ነፍስ በተፍጥሮ የምታዘነብልባቸውንና ምግብን መጠጥንና ወሲብን የመሳሰሉትን ነገሮች ከመውደድ ጋር አይጻረርም። ነቢዩﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹ከቅርቢቱ ዓለም ሕይወት ሴቶችና ሽቶ ለእኔ የተወደዱ እንዲሆኑ ተደርገዋል።››

(በአሕመድ የተዘገበ)

ስለዚህም ነቢዩﷺ የወዳዷቸው በመሆኑ በዱንያ ላይ እነሱን ማፍቀር ከሽርክና ከማጋራት ጋር የማይመደብ ነገሮች አሉ ማለት ነው። በዚህም መሰረት ሐራም እስካልሆነ ድረስ አንድ ሰው የዓለማዊ ሕይወት ጉዳዮች የሆኑትን ነገሮች ማፍቀር ይችላል።

4-

አላህን የሚወደውን ያህል ሌላውን የወደደ ሰው፣በአላህ ያጋራ ሙሽሪክ ነው። አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(وَمِنَ ٱلنَّاسِ مَن يَتَّخِذُ مِن دُونِ ٱللَّهِ أَندَادٗا يُحِبُّونَهُمۡ كَحُبِّ ٱللَّهِۖ وَٱلَّذِينَ ءَامَنُوٓاْ أَشَدُّ حُبّٗا لِّلَّهِۗ وَلَوۡ يَرَى ٱلَّذِينَ ظَلَمُوٓاْ إِذۡ يَرَوۡنَ ٱلۡعَذَابَ أَنَّ ٱلۡقُوَّةَ لِلَّهِ جَمِيعٗا وَأَنَّ ٱللَّهَ شَدِيدُ ٱلۡعَذَابِ ١٦٥)

‹‹እነዚያ ያመኑትም፣አላህን በመውደድ (ከነርሱ) ይበልጥ የበረቱ ናቸው፤እነዚያም የበደሉት ሰዎች ቅጣትን (በትንሣኤ ቀን) ባዩ ጊዜ፣ኃይል ሁሉ ለአላህ ብቻ መኾኑንና አላህም ቅጣቱ ብርቱ መኾኑን (በአዱኛ ዓለም) ቢያውቁ ኖሮ፣(ባላንጣዎችን በመያዛቸው በተጸጸቱ ነበር)።››

[አልበቀራህ፡165]

በዚህ አንቀጽ በአምልኮና በአክብሮት የአላህን ፍቅር ከሌላ ማናቸውም ፍቅር ጋር እኩል በሚያደርግ ሰው ላይ ብርቱ ማስጠንቀቂያ ተላልፏል።

‹‹ከሥራዎች ሁሉ ይበልጥ አላህ ዘንድ ተወዳጁ ለአላህ ብሎ መውደድና ለአላህም ብሎ መጥላት ነው።›› (በአሕመድ የተዘገበ)

አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(قُلۡ إِن كَانَ ءَابَآؤُكُمۡ وَأَبۡنَآؤُكُمۡ وَإِخۡوَٰنُكُمۡ وَأَزۡوَٰجُكُمۡ وَعَشِيرَتُكُمۡ وَأَمۡوَٰلٌ ٱقۡتَرَفۡتُمُوهَا وَتِجَٰرَةٞ تَخۡشَوۡنَ كَسَادَهَا وَمَسَٰكِنُ تَرۡضَوۡنَهَآ أَحَبَّ إِلَيۡكُم مِّنَ ٱللَّهِ وَرَسُولِهِۦ وَجِهَادٖ فِي سَبِيلِهِۦ فَتَرَبَّصُواْ حَتَّىٰ يَأۡتِيَ ٱللَّهُ بِأَمۡرِهِ)

‹‹፦ አባቶቻችሁና ወንዶች ልጆቻችው፣ወንድሞቻችሁም፣የሰበሰባችኋቸው ሀብቶችም፣መክሰሩዋን የምትፈሩዋት ንግድም፣የምትወዷቸው መኖሪያዎችም፣እናንተ ዘንድ ከአላህና ከመልክተኛው፣በርሱ መንገድም ከመታገል፣ይበልጥ የተወደዱ እንደኾኑ፣አላህ ትእዛዙን እስኪያመጣ ድረስ ተጠባበቁ፣በላቸው፤››

[አልተውባህ፡24]

የተዘረዘሩትን ስምንቱን ነገሮች ከአላህ ይበልጥ ለወደደ ሰው በዚህ አንቀጽ ብርቱ ማስፈራሪያ ተላልፎበታል። ከአነስ በተላለፈው መሰረት የአላህ መልክተኛﷺ እንዲህ ብለዋል ፦

‹‹እኔ ከልጁ ከአባቱና ከሰዎች ሁሉ ይበልጥ እርሱ ዘንድ የተወደድኩ እስክሆን ድረስ አንዳችሁ (የተሟላ እምነት) አያምንም።››

(በእብን ማጃህ የተዘገበ)

5-

ከምእመናን ሌላ ሙሽሪኮችን መውደድና ረዳቶች አድርጎ መያዝ፣በሙሽሪኩ ሃይማኖትና በማጋራቱ ምክንያት አላህንﷻ ከማፍቀር ጋር ይጻረራል። ለአላህ ብሎ መውደድና ለአላህ ብሎ መጥላት ከኢማን መሠረቶች ውስጥ አንዱ ጽኑ መሰረት ነው። አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(لَّا يَتَّخِذِ ٱلۡمُؤۡمِنُونَ ٱلۡكَٰفِرِينَ أَوۡلِيَآءَ مِن دُونِ ٱلۡمُؤۡمِنِينَۖ وَمَن يَفۡعَلۡ ذَٰلِكَ فَلَيۡسَ مِنَ ٱللَّهِ فِي شَيۡءٍ إِلَّآ أَن تَتَّقُواْ مِنۡهُمۡ تُقَىٰةٗ)

‹‹ምእምናን፣ከሓዲዎችን ከምእምናን ሌላ ረዳቶች አድርገው አይያዙ፤ይኸንንም የሚያደርግ ሰው፣ከአላህ (ሃይማኖት) በምንም ውስጥ አይደለም፤ከነርሱ መጠበቅን ብትጠበቁ እንጂ፤››

[ኣል ዒምራን፡28]

በዚህም ምእመናን ከሓዲዎችን የልብ ወዳጆችና ረዳቶች አድርገው እንዳይይዙ ተከልክለዋል። ይህን የሚያደርግ ሰው ከአላህ ሃይማኖት በምንም ውስጥ አይደለም። የሚያፈቅሩትን ማፍቀርና የርሱን ጠላት የሆነውንም ማፍቅር እርስ በርስ የሚጋጩ ነገሮች ናቸው።

(إِلَّآ أَن تَتَّقُواْ مِنۡهُمۡ تُقَىٰةٗ)

‹‹ከነርሱ መጠበቅን ብትጠበቁ እንጂ፤››

[ኣል ዒምራን፡28]

ያንን ካላደረጉ መልካም አብሮነት አይኖርም ብለው ከፈሩ ግን አላህﷻ እነሱን መወዳጀት ፈቅዷል። በዚህ ሁኔታ ልብ በኢማን እንደጸና እና እንደተረጋጋ ክሕደትና ከሓዲዎችን መጥላቱን እንደቀጠለ፣ላይላዩን ብቻ መወዳጀትና መቻቻልን መፍጠር ይፈቀዳል። አላህﷻ እንዲህ ብሏል ፦

(إِلَّا مَنۡ أُكۡرِهَ وَقَلۡبُهُۥ مُطۡمَئِنُّۢ بِٱلۡإِيمَٰنِ)

‹‹ልቡ በእምነት የረጋ ኾኖ (የክሕደት ቃል ለመናገር) የተገደደ ሰው ብቻ ሲቀር፤››

[አልነሕል፡106]

ነቢያችንﷺ በዱንያ ላይ ለዘለዓለም ከመኖርና አላህﷻ ከመገናኘት አንዱን እንዲመርጡ ሲደረጉ፦

‹‹(ምርጫዬ) የላይኛው ጓደኝነት (ከነቢያት ከጻድቃን፣ከሰማዕታትና ከደጋጎቸቹ ጋር መሆን) ነው።››

(በአሕመድ የተዘገበ)

በማለት ነቢዩﷺ ከዱንያ ፍቅርና ከመደሰቻዎቿ በማብለጥና በማስቀደም የአላህን ፍቅርና ከርሱ ጋር መገናኘትን መርጠዋል።

የአላህ ፍቅር ምልክቱ እርሱን በብዛት ማስታወስና ስሙን መዘከር፣ከርሱ ጋር መገናኘትን መናፈቅ ነው። አንድን ነገር ያፈቀረ ሰው አብዝቶና ደጋግሞ የሚያወሳው ሲሆን ከርሱ ጋር መገናኘትንም ይናፍቃል።

ረቢዕ ብን አነስ



Tags: